የመጸሐፍ ቅዱስ ጥናት መምሪያ

ለዚህ ሣምንት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት የሚከተሉትን ጥቅሶች ያንብቡ፡ ሕዝ. 28:15-16፣ ዘዳ. 4:44፣ ሮሜ 3:20፣ ዘዳ. 10:1–15፣ ዘዳ. 5:6–22፣ ዘዳ. 9:1–6።
የሣምንቱ ጥናት መሪ ጥቅስ “ ‘የእግዚአብሔርን ጸጋ አላቃልልም፤ ጽድቅ በሕግ በኩል የሚገኝ ከሆነማ፣ ክርስቶስ እንዲያው በከንቱ ሞተ ማለት ነዋ!” (ገላ. 2፡21)።
አ
ብዛኞቹ የክርስትና ኃይማኖቶች ስለ ሕግ እና ጸጋ የሚናገሩ
ሲሆን፤ በሁለቱ መካከል ያለውን ዝምድናም ያስተውላሉ። ሕጉ
የእግዚአብሔር ቅድስና እና ጽድቅ መመዘኛ ሲሆን፣ ይህን ሕግ መጣስ
ኃጢአት ነው። “ኃጢአት የሚያደርግ ሁሉ ዐመፅን ያደርጋል፤ ኃጢአትም
ዐመፅ ነው።” (1 ዮሐ. 3፡4)። እኛ ሁላችን ያንን ሕግ በመጣሳችን የተነሣ፡
“መጽሐፍ… ዓለም ሁሉ የኃጢአት እስረኛ መሆኑን ያውጃል” (ገላ. 3፡22)።
እኛን ሊያድን የሚችለው የእግዚአብሔር ጸጋ ብቻ ነው። “በእምነት በጸጋ
ድናችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም”
(ኤፌ. 2፡8)።
(ሰባተኛ ቀን ሰንበት የሕጉ ክፍል መሆኑን የሚያመላክት መጠነኛ ዝርዝር
መቅረቡ እሙን ነው። ሆኖም በዙዎቹ ክርስቲያኖች በተለያዩ ምክንያቶች
ለጊዜውም ቢሆን ሰባተኛውን ቀን ሰንበት ለመቀበል ሲቃወሙ ይታያሉ-ለተቃውሟቸው ከሚያቀርቧቸው ደካማ ማመካኛዎች ጋር! ለነገሩ ይህ ራሱን
የቻለ ሌላ ርዕሰ ጉዳይ ነው)
ምንም እንኳ የሕጉ እና የጸጋው ጭብጥ በተለያዩ መንገዶችና ክስተቶች
ቢገለጥም፣ የዘዳግም መጽሐፍን ጨምሮ በሁሉም የመጽፍ ቅዱስ ክፍሎች
መኖሩ እርግጥ ነው። የዘዳግም መጽሐፍም ቢሆን፣ በሕግና በፀጋ መካከል
ያለውን ግንኙነት ያቀርባል። ሆኖም አቀራረቡ ከተለመደው በተለየ ዐውድ
ነው።
እግዚአብሔር የፍቅር አምላክ ሲሆን፣ ፍቅር ደግሞ አጠቃላይ የባህሪውና
የመንግሥቱ መሠረት ነው። አጸፋዊ የፍቅር ምላሽ እንድንሰጠው የሚፈልገው
ይህ አምላክ፣ ሞራላዊ የመምረጥ ነጻነት ያላቸው ፍጡራን አድርጎ ማለትም
በፍቅር ውስጥ የሚገኘውን ነጻነት አጎናጽፎ ፈጠረን።
የመምረጥ ነጻነት ጽንሰ ሀሳብ አስኳል ምራላዊው ማለትም የማይለወጠው
አምላካዊ ሕግ ነው። አቶማዊ ቅንጣቶች፣ የባሕር ሞገዶች፣ ካንጋሮዎች፣
ተፈጥሯዊውን ሕግ ቢከተሉም፤ ሥነ ምግባራዊውን ሕግ ግን አይከተሉም
ወይም መከተል አያስፈልጋቸውም። እግዚአብሔር አምላክ በሰማይም እንኳ
ለመላእክት የሥነ ምግባር ሕግ ያለው ለዚህ ነው።
የሉሲፈርን በሰማይ መውደቅ የሚናገሩትን እነዚህን ጥቅሶቹ
ያንብቡ፡ ሕዝ. 28፡15-16። “ክፋት” ተገኘበት፣ “ኃጢአትም”
ሠራ። ከሰማይ ዐውድ አኳያ ጥቅም ላይ የዋሉት እነዚህ ቃላት
በሰማይ የሥነ ምግባር ሕግ ስለ መኖሩ ምን ያሳያሉ?
“ክፋት” እና “ኃጢአት” የተሰኙት ሁለቱም ቃላት በእኛ በሰዎች መካከል ጥቅም ላይ ውለዋል። ይሁን እንጂ አምላካዊው ቃል በሰማይ ማለትም በሌላው የፍጥረት ክፍል ውስጥ ለተከናወኑት ነገሮች ተመሳሳይ አገላለጽ ተጠቅሟል። ይህ ደግሞ በሰማይም ሆነ በምድር ስላሉት ነገሮች አንድ ነገር ሊነግረን ይገባል። “እንግዲህ ምን እንላለን? ሕጉ በራሱ ኃጢአት ነውን? በፍጹም አይደለም፤ ነገር ግን በሕግ በኩል ባይሆን ኖሮ፣ ኃጢአት ምን እንደ ሆነ ባለወቅሁም ነበር፤ ሕጉ ‘አትመኝ’ ባይል ኖሮ፣ ምኞት ምን እንደ ሆነ በእርግጥም አላውቅም ነበር።” (ሮሜ 7፡7)። ይህ ተመሳሳይ ጽንሰ ሀሳብ--ቢያንስ በመርኅ ደረጃ እንዴት በሥነ ምግባር የተሞሉ ፍጥረታት ማለትም መላእክት በሚኖሩበት ሰማይ ሊኖር ቻለ?
“የእግዚአብሔር ፈቃድ በቅዱሱ ሕጉ መመሪያዎች ውስጥ የተገለጠ ሲሆን፤
የዚህ ሕግ መርኅዎች ደግሞ የሰማይ መርኅዎች ናቸው። የሰማይ መላእክት
የእግዚአብሔርን ፈቃድ ከማወቅ የላቀ ዕውቀት ላይ አይደርሱም። በመሆኑም
የእርሱን ፈቃድ ማድረግ በሙሉ ኃይላቸው የሚሳተፉበት ከፍተኛው
አገልግሎት ነው።”—Thoughts From the Mount of Blessing, p. 109.
በሰማይም ሆነ በምድር እግዚአብሔር ነጻ የመምረጥ ነጻነት የሰጣቸው
ፍጡሮቹ የሚገዙበት የሥነ ምግባር ሕግ አለ። ይህን ሕግ መጣስ በሰማይም
ሆነ በምድር ኃጢአት ነው።
የሥነ ምግባር ሕግ ጽንሰ ሀሳብ የመምረጥ ነጻነት ባለቤት ከሆኑት
ፍጥረታት ጽንሰ ሀሳብ ጋር የማይነጣጠለው ለምንድን ነው? ሕጉ
ባይኖር ሥነ ምግባራዊው እና ኢ-ሥነ መግባራዊው እንዴት
ይገለጽ ነበር?
በከነዓን ድንበር ላይ የነበሩት በእግዚአብሔር የተመረጡ ዕብራውያን ሕዝቦች
በመጨረሻ እግዚአብሔር ቃል የገባላቸውን ምድር ለመውረስ ተቃረቡ።
ቀደም ብለን እንደ ተመለከትነው፣ ኦሪት ዘዳግም ዕብራውያን ምድሪቱን
ከመውረሳቸው አስቀድሞ ሙሴ የሰጣቸውን የመጨረሻዎቹን መመሪያዎች
የያዘ መጽሐፍ ነው። በእነዚያ መመሪያዎች ውስጥ እንዲታዘዟቸው
የተሰጧቸው ትእዛዞች ተካተው ነበር።
የሚከተሉትን ጥቅሶች ያንብቡ። በተደጋጋሚ የተወሳው ነጥብ
ምንድን ነው? ይህ ነጥብ ለህዝቡ ያን ያህል አስፈላጊ የሆነውስ
ለምንድን ነው? (ዘዳ. 4:44፣ ዘዳ. 17:19፣ ዘዳ. 28:58፣ ዘዳ.
30:10፣ ዘዳ. 31:12፣ ዘዳ. 32:46፣ ዘዳ. 33:2)
የዘዳግም መጽሐፍን በችኮላ እንኳ ቢያነቡት ለእስራኤላውያን ሕጉን መታዘዝ
ምን ያህል ወሳኝ እንደ ነገር ለመረዳት አያዳግትም። በእርግጥም የቃል
ኪዳን ግዴታዎቻቸው ነበሩ። እነርሱ ለራሳቸው ሊያደርጉ የማይችሏቸውን
ብሎም የማይገባቸውን ስፍር ቁጥር የሌላቸውን አያሌ ነገሮች እግዚአብሔር
አድርጎላቸዋል ወደፊትም ማድረጉን ይቀጥላል (ይህ ከእግዚአብሔር
የምናገኘው የማይገባን ስጦታ--ጸጋ ነው)። እርሱ በምላሹ የጠየቃቸው ነገር፡
ሕጌን ታዘዙ--የሚል ነበር፡፤፡
አሁን ያለውም ከቀድሞው የተለየ አይደለም። የሚያድነን ሕግ መጠበቅ
ሳይሆን የእግዚአብሔር ጸጋ ነው--“ማንም ሰው ሕግን በመፈጸም ሳይሆን፣
በእምነት እንደሚጸድቅ እናረጋግጣለን” (ሮሜ 3፡28)። ሆኖም እኛ ምላሽ
የምንሰጠው ሕጉን በመታዘዝ ነው። ሕጉን የምንጠብቀው ከንቱ የመዳን ሙከራ
ለማድረግ አይደለም። “ስለዚህ ሕግን በመጠበቅ ማንም ሰው በፊቱ ጻድቅ ነው
ሊባል አይችልም፤ ይልቁንም በሕግ አማካይነት ኃጢአትን እንገነባለን” (ሮሜ
3፡20)። ነገር ግን አብልጦ በጸጋ ከተሰጠን ደኅንነት የተነሣ ነው። “ብትወዱኝ
ትእዛዜን ጠብቁ” (ዮሐ. 14፡15 /1962 ትርጉም/)።
ኦሪት ዘዳግም የጸጋ እና ሕግ አበይት አስተምህሮዎችን የያዘ መጽሐፍ ተደርጎ
መታየት ይችላል። እግዚአብሔር በጸጋው እኛን ዋጅቶ ለራሳችን ማድረግ
የማንችለውን ሲያደርግልን (እስራኤላውያን በራሳቸው ከግብፅ ማምለጥ
የማይሆንላቸውን ያህል) በምላሹ በእምነት--እርሱንና ሕጉን የመታዘዝ
ሕይወት እንኖራለን። ከአዳም ውድቀት አንስቶ ወደፊት እስከሚገለጠው
የመከራ እና የአውሬው ምልክት ዘመን የሚኖሩ ሕዝቦች ተለይተው
የተገለጹት፡ “የእግዚአብሔርን ትእዛዛት የሚጠብቁት ኢየሱስንም በማመን
የሚጸኑት ቅዱሳን ትዕግሥታቸው በዚህ ነው።” (ራእ. 14፡12 /1962 ትርጉም/)
በሚል ነው። እግዚአብሔር ከቃል ኪዳኑ ሕዝቦች ጋር ያለው ግንኙነት ከሕግ
እና ጸጋ ጋር የተሳሰረ ነው። አምላካዊው ጸጋ ሕጉን በመጣሳችን ይቅር ሲለን፤
ይኸው ጸጋ ሕጉን እንድንታዘዝ ያስችለናል። መታዘዛችን ከእርሱ ጋር የገባነው
ቃል ኪዳናዊ ግንኙነት ነው።
ለሕጉ ስንታዘዝ ሳለ ሕጋውያን ከመሆን ወጥመድ መጠበቅ
የምንችለው እንዴት ነው?
መጽሐፍ ቅዱስን ላለመቀበል ምክንያት የሚፈልጉ ተጠራጣሪዎች ብዙውን
ጊዜ በብሉይ ኪዳን የሚገኙ አንዳንድ ጠንካራ አምላካዊ ቃላት ላይ ጣታቸውን
ይቀስራሉ። ሀሳቡ የብሉይ ኪዳኑን አምላክ በተለይ ከየሱስ ጋር እያነጻጸሩ-ጨካኝ፣ በቀለኛና ተንኮለኛ አድርጎ ማቅረብ ነው። ይህ አዲስ የሙግት
ሀሳብ አይደለም። ይልቁንም እንደ ዛሬው ሁሉ ከብዙ መቶ ዓመታት በፊት
ለመጀመሪያ ጊዜ ሲተዋወቅም በኅፀፅ የተሞላ ነበር።
ጌታ የጥንት እስራኤላውያን ሕዝቦቹን እንደሚወድና ሁሌም ቢሆን
ምርጥ የሆነውን ለእነርሱ እንደሚመኝ የብሉይ ኪዳን መጽሐፍ በተደጋጋሚ
ይናገራል። ይህ ፍቅር በዘዳግም መጽሐፍ በብርቱ ተገልጧል።
ጥቅሶቹን ያንብቡ፡ ዘዳ. 10፡1-15። የመልእክቶቹ ቀዳሚ ዐውደ
ሀሳብ ምንድን ነው? ኃጢአት ከሠሩ በኋላም እንኳ እግዚአብሔር
ለሕዝቡ ስለነበረው ስሜት ምን ያስተምሩናል? በእርግጥ--ስለ ጸጋ
ያስተምሩናል?
እግዚአብሔር ለእስራኤል የነበረው ጸጋ እና ፍቅር ከእነዚህ ጥቅሶች
ይንቆረቆራል። በተለይ ቁ. 12 እና 13 ልብ ይበሉ። ጥቅሶቹ አንድ ረጅም ዐረፍተ
ነገርና ጥያቄ የያዙ ሲሆን፣ ጥያቄው ቀላል ነው፡ እኔ አምላክህ አግዚአብሔር
ከአንተ የምፈልገው ምንድን ነው…በመንገዶቼ ሁሉ እንድትሄድ፣ እንድትወደኝ፣
እንድታገለግለኝና ትእዛዞቼንና ሥርዓቶቼን እንድትጠብቅ አይደለምን?
በዕብራይስጥ ቋንቋ መላው እስራኤል “የአንተ” እና “አንተ” በሚል ነጠላ
ቃል ተገልጾአል። ምንም እንኳ እግዚአብሔር በእርግጠኝነት እየተናገረ ያለው
ስለ አጠቃላዩ ሕዝብ ቢሆንም፣ ሆኖም ሰዎች በተናጥል ካልታዘዙ ቃላቱ ምን
ፋይዳ ይኖራቸዋል? አጠቃላዩ--የእያንዳንዱ ተናጥል ድምር ውጤት ነው።
ጌታ እስራኤልን እንደ ሕዝብ ሲናገር፣ እያንዳንዱን ግለሰብ በግለሰብ ደረጃ
እየተናገረ ነበር።
በቁ. 13 መጨረሻ የቀረቡትን፡ “መልካም እንዲሆንልህ” የሚሉትን ቃላት
መዘንጋት አንችልም። በሌላ አነጋገር ሕዝቡ ለአምላካዊው ፈቃድ እንዲገዛ
እግዚአብሔር እያዘዘ የነበረ ሲሆን፣ ይህ ደግሞ ለእነርሱው ጥቅም ነበር።
እነርሱን የፈጠረ፣ ደግፎ የያዘና የሚበጃቸውን የሚያውቀው አምላክ፣ ምርጥ
የሆነው ነገር ሁሉ ባለቤት ይሆኑ ዘንድ ይፈልጋል። ሕጉን መታዘዝ፣ አሥርቱን
ቃላት መጠበቅ ፋይዳው ለራሳቸው ጥቅም ብቻ ነው።
ሕጉ ብዙውን ጊዜ ከቅጥር፣ ከመጠበቂያ ግድግዳ ጋር በንጽጽር የሚቀርብ
ሲሆን፤ ተከታዮቹ በቅጥሩ ውስጥ ሲቆዩ ሊያጠፏቸው ከሚችሉ ክፉ
መናፍስት ግፊት የተጠበቁ ይሆናሉ። በአጭሩ እግዚአብሔር ለሕዝቡ ካለው
ፍቅር የተነሣ ሕጉን ሰጠ። እርስዎ ሕጉን የሚታዘዙት ለራስዎ “መልካም
እንዲሆንልዎ” ነው።
የእግዚአብሔርን ሕግ የምንታዘዘው በእርግጥም ለራሳችን “መልካም
እንዲሆንልን” ነው ካልን፣ ይህን መመልከት የምንችልባቸው
መንገዶች የትኞቹ ናቸው?
በኦሪት ዘዳግም መጽሐፍ አንድ ርዕሰ ጉዳይ ተደጋግሞ የቀረበ ሲሆን፣ ይኸውም
ጌታ እስራኤል ሕዝቡን ከግብፅ ምድር መቤዠቱን ይመለከታል። እነዚህ
ሕዝቦች እግዚአብሔር ያደረገላቸውን ነገር እንዲያስታውሱ በተደጋጋሚ
ተነግሯቸዋል፡ “ ‘ “ከዚህ የተነሣ እግዚአብሔር በብርቱ እጅና በተዘረጋች
ክንድ፣ በታላቅ ድንጋጤ፣ በታምራዊ ምልክትና በድንቅ ከግብፅ አወጣን” ’ ”
(ዘዳ. 26፡8፣ ዘዳ. 16፡1-6)።
መላውን ብሉይ ኪዳን የሚያካትተው የእስራኤላውያን በታላቅ ኃይል
ከግብፅ መውጣት ታሪክ፣ የኃያሉ አምላክ ከግብፅ ባርነት እና ጭቆና በጸጋው
ማዳን ምሳሌ ነው፡ “ከግብፅ አወጣሁህ፣ ከባርነት ምድርም ተቤዠሁህ” (ሚክ.
6፡4)።
በክርስቶስ ላይ በሚኖር እምነት የሚገኝ ደኅንነት ምሳሌ የሆነው በታላቅ
ኃይል ከግብፅ መውጣታቸው፤ እነሆ በአዲስ ኪዳንም የምናገኘው ጽንሰ ሀሳብ
ነው። “ሕዝቡ በደረቅ መሬት እንደሚኬድ ቀይ ባሕርን በእምነት ተሻገሩ፤
ግብፃውያን ግን እንደዚሁ ለማድረግ ሲሞክሩ ሰጠሙ።” (ዕብ. 11፡29፣ 1ቆሮ.
10፡1-4)።
ሙሴ ሕጉን፣ አሥርቱን ትእዛዛትና ከያሕዌ ጋር የገቡትን
ቃል ኪዳን በድጋሚ የሚያቀርብበትን ዘዳ. 5: 6–22 ያንብቡ።
አራተኛውን ትእዛዝ እና ትእዛዙ በዚህ ስፍራ የተሰጠበትን
ምክንያት ልብ ይበሉ። የሕግን እና ጸጋን ተጨባጭ እውነታ
በሚገልጽ መልኩ ምን ተብሏል?
ሙሴ በሰባተኛው ቀን ሰንበት ስለ ማረፍ የተሰጠውን መሠረታዊ ትእዛዝ
ከተጨማሪ እጽንኦት ጋር በድጋሚ ያቀርባል። ምንም እንኳ በድንጋይ
ጽላቶች ተጽፈው በዘፀአት ተሰጥቷቸው የነበረ ቢሆንም፣ እዚህ ላይ ሙሴ
ያንኑ የተሰጠውን አስፋፍቶ ሲያቀርብ ይታያል። ይኸውም እንደ ፍጥረት
መታሰቢያ ብቻ ሳይሆን ከግብፅ የመቤዠታቸው መታሰቢያ ጭምር አድርገው
እንዲመለከቱት ነው። የእግዚአብሔር ጸጋ ከግብፅ ዋጅቶ ከሥራቸው
የሚያርፉበትን ዕድል ሰጣቸው (ዕብ. 4፡1-5)። አሁን፣ እግዚአብሔር
ለሰጣቸው ጸጋ በጎ ምላሽ ይሆን ዘንድ ይህንኑ ጸጋ ለሌሎች ማስተላለፍ
ይኖርባቸዋል።
ከዚህ አኳያ ሰባተኛው ቀን ሰንበት የአምላካዊው ፍጥረት ሥራ ብርቱ ምሳሌ
ብቻ ሳይሆን የመዋጀትና የጸጋም ብርቱ ምሳሌ ይሆናል። በቤት ውስጥ ካሉ
ህጻናት ውጪ አገልጋዮች፣ እንስሶች ብሎም አብረው የሚኖሩ መጻተኞች
ማረፍ ይችላሉ። ሰንበት ለአይሁድ የተሰጠውን ጸጋ ለሌሎች ማለትም ከኪዳኑ
ሕዝቦች ውጭ ላሉት ጭምር ይሰጣል። ሕጉ በእግዚአብሔር ትእዛዛት አማካይ
ስፍራ ላይ ይገኛል። እግዚአብሔር በቸርነቱ ያደረጋቸውን እነርሱም ለሌሎች
ማድረግ ይጠበቅባቸዋል። ጉዳዩ ያን ያህል ቀላል ነው።
ጥቅሶቹን ያንብቡ፡ ማቴ. 18፡21-35። በዚህ ተምሳሌታዊ ታሪክ
የቀረበው መርኅ በሰንበት ትእዛዝ ውስጥ የተገለጸበት መንገድ ምን
ይመስላል--በተለይ በዘዳግም ከተሰጠው አጽንኦት አኳያ?
መጽሐፍ ቅዱስን የእምነታቸው መሠረት አድርገው ለተቀበሉ የሁሉም
ክርስትና እምነቶች ማዕከል የሆነው አስተምህሮ በእርግጥም ታላቁ የጽድቅ
በእምነት ርዕሰ ነጥብ ነው። “መጽሐፍስ ምን ይላል? አብርሃም እግዚአብሔርን
አመነ ጽድቅም ሆኖ ተቆጠረለት” (ሮሜ 4፡3)።
“በእምነት መጽደቅ ምን ማለት ነው? የሰውን ክብር ትቢያ ላይ ጥሎ ሰው በራሱ
ኃይል ሊያደርግ የማይችለውን ማድረግ የእግዚአብሔር ሥራ ነው። ሰዎች
የራሳቸውን ከንቱነት ሲያዩ የክርስቶስን ጽድቅ ለመልበስ ዝግጁ ይሆናሉ።
”—
Ellen G. White, The Faith I Live By, p. 109.
እግዚአብሔር ማን እንደሆነና እርሱ ምን ያህል ቅዱስ እንደሆነ ሲያስቡና
በተቃራኒው የእኛን ማንነትና ምን ያህል የረከስን እንደሆንን ሲገነዘቡ--እኛን
ለማዳን አስደናቂ የጸጋ እርምጃ መወሰድ ይኖርበታል። ተወሰደም፡ እንከን
ዐልባው ንጹሁ ክርስቶስ ስለ በደለኞች በመስቀል ላይ ሲሞት ሳለ የጸጋ ተግባር
ገቢራዊ ሆነ።
ይህን ዐውደ ሀሳብ በአእምሮዎ እንደያዙ እነዚህን ጥቅሶች ያንብቡ፡
ዘዳ. 9፡1-6። እዚህ ላይ ሙሴ ለማይገባቸው ስለ ተገለጠው
አስደናቂ አምላካዊ ጸጋ ተጨባጭ እውነታ ዙሪያ ለሕዝቡ ምን
እያለ ነው? በዚህ ስፍራ የሆነው ነገር የጽድቅ በእምነትን መርኅ
እንዴት ያንጸባርቃል?
አንድ ሰው የጳውሎስን የወንጌል አስተምህሮ እንደሚከተለው በአጭሩ
ሊያስቀምጥ ይችላል፡ እግዚአብሔር የሚያድንህ “ከጽድቅህ ወይም ከልብህ
ቅንነት የተነሣ” አይደለም (ዘዳ. 9፡5)። ይልቁንም ይህን የሚያደርገው ከ
“ዘላለማዊው ወንጌል” (ራእ. 14፡6) የተስፋ ቃል የተነሣ ነው። “እኛ ስላደረግነው
አንዳች ነገር ሳይሆን ከዕቅዱና ከጸጋው የተነሣ ያዳነን ወደ ቅዱስ ሕይወትም
የጠራን እርሱ ነው። ይህም ጸጋ ከዘላለም፣ ከዘመናት በፊት በክርስቶስ ኢየሱስ
ተሰጠን” (2ጢሞቴ. 1፡19፣ ቲቶ 1፡2)። የተስፋ ቃሉ “ከዘመናት በፊት” እስከ
ተሰጠንና እኛ “ከዘመናት በፊት” ጭራሹኑ እስካልተፈጠርን ድረስ በእርግጥም
በሥራችን ሊሆን አይችልም።
በአጭሩ--ስህተትና ጉድለት የሚገኝብዎት አንገተ ደንዳና ቢሆኑም፣
ጌታ ይህን ድንቅ ሥራ ለእርስዎ እና በእርስዎ ይሠራል። በመሆኑም ጌታ
እርሱን እንዲታዘዙና ትእዛዛቱን እንዲጠብቁ ያዝዎታል። እነሆ የተስፋ ቃሉ
አስቀድሞውኑ ተሰጥቶዎታል፡ ሥራዎ፣ መታዘዝዎ የቱንም ይህል መልካም
ሊሆን ቢችልም (አይደለም) ሊያድንዎ አይችልም። ይልቁንም እነዚህ ነገሮች
ውጤት ናቸው።
ጌታ በጸጋ አድኖዎታል። አሁን በልብዎ ጽላት በተጻፈው ሕጉ
እና መንፈሱ በሚሰጥዎት ኃይል እየታገዙ ሕጉን መታዘዝዎን
ይቀጥሉ።
“በሰማይ በእግዚአብሔር ሕግ ላይ ያመጸው የክርስቶስ
ጠላት እንደ አንድ ስልጡን የጦር አበጋዝ ብቸኛውን ኃጢአትን ገለጾ
የሚያሳየውንና የጽድቅ መለኪያ መሣሪያ የሆነውን የእግዚአብሔር ሕግ ከንቱ
ለማድረግ ፍጹም ማታለል በተሞላበት አካሄድ አንዱን ከሌላው እያማታ
በሚችለው አቅሙ ሠርቷል።””—Ellen G. White, Review and Herald,
November 18, 1890.
ሁለት ትሪሊዮን ጋላክሲዎች በጠፈር ውስጥ ያንጸባርቃሉ። እያንዳንዱ ጋላክሲ
አንድ መቶ ቢሊዮን 100,000,000,000 ከዋክብት አቅፎ ይዟል። እያንዳዳቸው
100 ቢሊዮን ከዋክብት የሚይዙት የሁለት ትሪሊዮን ጋላክሲዎች የከዋክብት
ብዛት ይህን ይመስላል፡ 200,000,000,000,000,000,000,000።
ማንኛውም ጸንሶ አንድ ነገር የሚፈጥር አካል ከተጸነሰው ወይም ከተፈጠረው
ነገር የበለጠ እና የላቀ ማንነት ሊኖረው ይገባል። በፒካሶ ከተሠሩ የሥነ ጥበብ
ሥራዎች ሁሉ ፒካሶ የላቀ ነው። ጠፈርን የጸነሰውና የፈጠረው አምላክም
እንዲሁ ከጠፈርና ሙላቱ የላቀ መሆን ይኖርበታል።
ይህን በልቦናዎ እንደያዙ ስለዚህ ጥቅስ አሰብ ያድርጉ፡ “በመጀመሪያ ቃል
ነበረ፤ ቃልም ከእግዚአብሔር ጋር ነበረ፤ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ። እርሱም
በመጀመሪያ ከእግዚአብሔር ጋር ነበረ። ሁሉ ነገር በእርሱ ተፈጥሯል፤
ከተፈጠረው ሁሉ ያለ እርሱ የተፈጠረ ምንም የለም።” (ዮሐ. 1፡1-3)። ይህ
ማለት፣ የተፈጠሩትን ነገሮች ሁሉ የፈጠረው እግዚአብሔር አምላክ እነዚያን
200,000,000,000,000,000,000,000 ከዋክብት እና ማንኛውንም ነገር
ፈጠረ።
ምን አደረገ? እጅግ ዝቅ ብሎ ሰብዓዊውን አካል ወሰደ፣ ህጻን ሆኖ
ተወለደ፣ ኃጢአት ዐልባ ህይወት ኖረ፣ እኛ የዘላለማዊ ህይወት ተስፋ ይኖረን
ዘንድ የሁላችንንም የኃጢአት ቅጣት ተሸክሞ በመስቀል ላይ ተሰቀለ።
ይህ ታላቅ እውነት ከፊታችን አለ፡ በመስቀል ላይ በየሱስ ክርስቶስ የተሰጠን
ጸጋ። ታዲያ እግዚአብሔር በምላሹ ምን እንድናደርግ ይጠይቀናል? “እነሆ፤
ሁሉ ነገር ከተሰማ ዘንድ፣ የነገሩ ሁሉ ድምዳሜ ይህ ነው፤ እግዚአብሔርን
ፍራ፤ ትእዛዙንም ጠብቅ፤ ይህ የሰው ሁለንተናዊ ተግባሩ ነውና።” (መክ. 12፡
13)።
1.ወደ እሁድ ጥናት መጨረሻ ላይ ያምሩ። የእግዚአብሔርን
ሕግ (አራተኛውን ትእዛዝ ጨምሮ) ማለትም አሥርቱን ትእዛዛት
መጠበቅ እንዳለባቸው የሚያምኑ ሰዎች የሕጋዊነትን ስውር ወጥመድ
ማስወገድ የሚችሉት እንዴት ነው? መታዘዝ፣ እንደውም ጥብቅ
የሆነውና የማይዋልለው መታዘዝ ከሕጋዊነት እንዴት ይለያል?
በሁለቱ መካከል ያሉ ልዩነቶችን ማወቅ የምንችለውስ እንዴት
ነው?
2.አሥርቱን ትእዛዛት የጣሱ ሰዎች ስለ ደረሰባቸው አስከፊ መዘዝ
የሰሟቸው ወይም በግል የሚያቋቸው ታሪኮች ካሉ ቢያጋሩ።
ሕጉ እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፍቅር በተጨባጭ ማንጸባረቁን
አስመልክቶ ይህ ምን ሊያስተምረን ይገባል?
3.በራሳችን መንገድ መንግሥተ ሰማይን ለመውረስ የምናደርገው
መፍጨርጨር ከንቱ መሆኑን መስቀሉ ሊያሳየን የሚገባው
ለምንድን ነው?