የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት መምሪያ

ለዚህ ሳምንት ጥናት የሚከተሉትን ጥቅሶች ያንብቡ፡- ዘፍ. 3:15፣ ዘሌ. 20:26፣ 1 ሳሙ. 2:2፣ 1 ዮሐንስ 4:7-19፣ ዘፍ. 1:1፣ ዘፍ. 2:7፣ ማቴ. 1:23፣ ማቴ. 28:20
የመታሰቢያ ጥቅስ፡ “እውነተኛ አምላክ ብቻ የሆንህ አንተን የላክኸውንም ኢየሱስ ክርስቶስን ያውቁ ዘንድ ይህች የዘላለም ሕይወት ናት።” ዮሐ. 17፡3
የእግዚአብሔርን ባሕርይ ግልጽ በሆነ መልኩ መረዳት ከእርሱ ጋር ጠንካራ ግንኙነት
ለመፍጠር መሠረት ነው። ለዚህም ነው በዚህ ሳምንት መጽሐፍ ቅዱስ ስለ እግዚአብሔር
ባሕርይ የሚናገረውን በጥንቃቄ የምንመለከተው፤ ምክንያቱም “ዓለማችንን የሸፈናት
እግዚኣብሔርን በሚገባ ያለመረዳት ጨለማ ነው። የእግዚአብሔርን ባህርይ በደንብ
ባለመረዳትና በትክክለኛው ባለመተርጎም ሰዎች የእርሱን ባህርይ የሚያውቁበት መጠን
እየቀነሰ መጥቷል። በዚህ ዘመን ከእግዚአብሔር የሆነ መልዕክት መታወጅ አለበት ። ይህም
በተጽዕኖው ጨለማውን የሚያበራ፡ በማዳኑ ደግሞ ኃያል የሆነ መልዕክት ነው። የአምላክ
ባህርይ በግልጽ ሊታወቅ ይገባል። በዓለም ጨለማ ውስጥ የእርሱ የክብሩ፣ የመልካምነቱ፣
የምህረቱና የእውነቱ ብርሃን ሊበራ ያስፈልገዋል። . . . የአምላካችን የፍቅር ባህሪው
የመጨረሻው የምህረት ብርሃን ጨረር ሆኖ ለዓለም እንዲታይ ተደርጎ መሰጠት አለበት” ኤለን
ጂ. ኋይት፣ የክርስቶስ ምሳሌያዊ ትምህርቶች፣ ገጽ 230-231(በአማርኛው)።
እግዚአብሔርን በበቂ ሁኔታ መግለጽ የማይቻል ይመስላል፣ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ
እርሱ የሚናገረውን ብቻ ማመልከት የተሻለው አማራጭ ነው። ምንም እንኳን በተለይ አሁን
ስለ እግዚአብሔር ድንቅ ባህሪ ማወቅ ያለብንን ሁሉ ባናውቅም፣ ስለ እርሱ የበለጠ ስንማር፣
ስለ እርሱ ያለን ግንዛቤ እና ፍቅር እየጠነከረ እንዲሄድ እንጸልይ፣ በዋናነትም ለሌሎች
ፍቅሩን እና ባህሪውን ለማንፀባረቅ ወደ እርሱ መቅረብ ያስፈልገናል።
*ለሚያዝያ 3 ሰንበት ለመዘጋጀት የዚህን ሳምንት ትምህርት ያጥኑ።
መጽሐፍ ቅዱስ ስለ እግዚአብሔር እውነተኛ፣ ግልጽ እና ወጥ የሆነ ምስል ይሰጣል።
መላው መጽሐፍ ቅዱስ በሚታየው ዓለማችን እና በማይታየው መካከል ያለውን
የማይታየውን መጋረጃ ለመክፈት ይፈልጋል፤ ከየት እንደመጣን እና ወዴት እንደምንሄድ
ለማሳየት፤ እና በመጨረሻም ማን እየተቆጣጠረ እንዳለ እና ምን እንደሚመስል ለማሳየት።
ከዘፍጥረት እስከ ራዕይ፣ በመጽሐፍ ቅዱስ እና ሥጋ በለበሰው አምላክ በኢየሱስ
ክርስቶስ አማካኝነት ራሱን ለእኛ ስለሚገልፀው አንድ እውነተኛ አምላክ እናነባለን። ስለ
እግዚአብሔር ሁሉን ቻይነት (ኢዮብ 1:12)፣ ሁሉን አዋቂነት (ኢሳ. 46:9, 10)፣ ፍትሐዊነት
(ኢሳ. 30:18)፣ ስለ ምሕረቱ (ዘዳ. 7:9)፣ ከእኛ ጋር ስላለው ፍቅሩ፣ ደግነቱና ትዕግስቱ
(ሮሜ. 2:4)፣ ስለ ጥበቡ (1ኛ ቆሮ. 2:7)፣ ስለ ጸጋው (2ኛ ቆሮ. 12:9)፣ ስለ ይቅርታው (ማቴ.
6:14)፣ ለሕይወታችን ስላለው ፈቃድ (ኤር. 29:11)፣ ሞትን ስለማሸነፍ ኃይሉ (ዮሐንስ
11:25)፣ ስለ ንግሥናው (መዝ. 47:8)፣ ስለ ዘላለማዊ ተፈጥሮው (ዘዳ. 33:27) እና እርሱን
እንድንወደውና ዘላቂ ግንኙነት እንዲኖረን የሚያደርጉንን ሌሎች በርካታ ባህሪያት ማንበብ
እንችላለን። ስለ እግዚአብሔርና ስለ እርሱ ማንነት ባወቅን ቁጥር፣ የበለጠ እንወደዋለን እና
ከእርሱ ጋር የቀረበና ዘላቂ ግንኙነት እንሻለን።
የእግዚአብሔርን ባሕርይ ለመጀመሪያ ጊዜ የተጠራጠረው ሉሲፈር ነበር። ስለ
እግዚአብሔር ማንነት የነበረው ጥርጣሬ በምድራችን ታሪክ ውስጥ ወደ ትልቁ ጦርነት
መራው። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ፣ “የሰዎች አእምሮ የእግዚአብሔርን እውቀት እንዳያገኙ
በሚከለክሉ ነገሮች እንዲጠመድ ማድረግ የሰይጣን የማያቋርጥ ጥናትና ትጋት ሆነ።”—ኤለን
ጂ. ኋይት፣ የቤተ ክርስቲያን ምክሮች፣ ጥራዝ 5፣ ገጽ 740። ሰይጣን ትክክለኛ እስካልሆነ
ድረስ ስለ እግዚአብሔር ያለን ምስል ምንም አይነት ቢሆን ግድ የለውም (ፓንቴይዝም፣
አምላክ የለሽነት፣ ዴዪዝም፣ ወዘተ)።
ዘፍጥረት 3:1-5ን ያንብቡ። ሉሲፈር ከሔዋን ጋር ባደረገው ውይይት ውስጥ የሉሲፈር
ግብ ምን ነበር? ለሔዋን ስለ እግዚአብሔር ባህሪ ምን አይነት ውሸት ነገራት?
በዋናነት ሰይጣን ለሔዋን የሰጠው መልእክት ይህ ነበር፡ እግዚአብሔር ከእናንተ ምስጢር
እየደበቀ ነው። እግዚአብሔር ለእናንተ የተሻለ ነገር እንዲሆንላችሁ አይፈልግም። በእርሱ ላይ
መታመን አትችሉም። ኤለን ኋይት በዚህ ላይ ሰፋ አድርጋ ስትናገር፣ “ከታላቁ ተጋድሎ መነሻ
ጀምሮ የእግዚአብሔርን ባህሪ በተሳሳተ መንገድ መግለጽ እና በሕጉ ላይ ዓመፅን ማነሳሳት
የሰይጣን ዓላማ ነበር” ብላለች።— የሃይማኖት አባቶችና ነቢያት፣ ገጽ 338።
የእግዚአብሔር ባሕርይ በአለማችን ውስጥ በተሳሳተ መንገድ እየተገለፀ ያለው እንዴት ነው?
ከሁሉም በላይ ደግሞ፣ እኛ አንዳንድ ጊዜ የእሱን ባህሪ ለሌሎች በተሳሳተ መንገድ ገልፀን ይሆን?
ቅድስና ሰዎች በዕለት ተዕለት ቋንቋቸው ብዙ ጊዜ የሚጠቀሙበት ቃል አይደለም፤ ምናልባትም በዙሪያችን በጣም ጥቂት ቅዱስ ነገሮች ስላሉ ሊሆን ይችላል። ከጊዜ አንፃር ሰንበት የተቀደሰ ቀን ነው፤ እግዚአብሔርም በእርግጥ ቅዱስ ነው። ነገር ግን የዕለት ተዕለት ሕይወታችን ከቅድስና የጎደለ ነው። ከእግዚአብሔር ባሕርይ ጋር ብዙ ጊዜ የተያያዙትን ባህሪያት ጥናት ብታደርጉ ቅድስና የእግዚአብሔር ማንነት ማዕከል መሆኑን ትገነዘባላችሁ። ግን ያ ምን ማለት ነው? የሚከተሉት ምንባቦች እግዚአብሔርን እንዴት ይገልፁታል? ዘሌዋውያን 20፡26፣ 1ኛ ሳሙኤል 2፡2፣ ኢሳይያስ 57፡15፣ እና ሕዝቅኤል 38፡23?
መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔርን የቅድስና ምሳሌ አድርጎ ሲገልጸው፣ እሱ ከክፋትና
ከኃጢአት ሙሉ በሙሉ የፀዳ እና የተለየ ነው ማለት ነው። እግዚአብሔር ከመጀመሪያ
እስከ መጨረሻ መቶ በመቶ መልካም ነው። በዚህ መልኩ፣ የእግዚአብሔር ቅድስና የሌሎች
ባሕርያቱ ሁሉ መሠረት ነው።
ለምሳሌ፣ የእግዚአብሔር ፍቅር ንፁህና ቅዱስ ፍቅር ነው - ከሁሉም ራስ ወዳድነት
ኃሳቦች ሙሉ በሙሉ የጸዳ ፍቅር ነው። ሁሉን አዋቂነቱ ቅዱስ ሁሉን አዋቂነት ነው፣
ማለትም ከክፉ ዓላማ የጸዳ ነው። እርሱ ቅዱስ ባይሆን ኖሮ ሁሉን አዋቂ በሆነው አምላክ
እንተማመን ነበር? በምትኩ፣ በጣም እንፈራው ነበር።
የእግዚአብሔር ሁሉን ቻይነት ቅዱስ ሁሉን ቻይነት ነው። ሁሉን ቻይ የሆነ ግን ቅዱስ
ያልሆነን አምላክ በምናብዎ ይሳሉ።
ኃያል፣ ክፉ አምባገነን ሊሆን ይችል ነበር። በእውነት እንድንወደው የሚያስችለን
የእግዚአብሔር ቅድስና ብቻ ነው። ምክንያቱም ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ እርሱ መልካም
ነው። ለዚህም ነው ቅድስና ስለ እግዚአብሔር ባህሪ ለመረዳት በጣም አስፈላጊው ባህሪ
የሆነው። ሆኖም፣ ምናልባት፣ በጣም በስህተት ከተስተዋሉት ባህርያት አንዱ ሊሆን ይችላል።
ወደ እግዚአብሔር ፊት የመጡትን እንደ ሙሴ፣ ኢሳይያስ፣ ሕዝቅኤል፣ ዳንኤል እና
ዮሐንስ ያሉ የመጽሐፍ ቅዱስ ገጸ-ባህሪያትን ያስቡ።
የመጀመሪያ ምላሻቸው ምን ነበር? ጫማቸውን አወለቁ፣ ፊታቸውን ደበቁ ወይም
እንደሞተ ሰው ሆኑ። እንደ ሰው፣ ኃጢአተኞች እና ንፁህ ያልሆንን ስለሆንን በእግዚአብሔር
ፊት መቆም አንችልም። የእግዚአብሔርን ፊት የሚያይ ማንኛውም ሰው በሕይወት
አይኖርም። በተመሳሳይ፣ ኤለን ጂ. ኋይት ራእይ ስታይ፣ ብዙ ጊዜ “ቅዱስ… ቅዱስ… ቅዱስ”
ትል ነበር፣ ምክንያቱም ያየችውን አብዛኛውን የሚገልፀው ያ ቃል ስለነበረ ሊሆን ይችላል።
ደግሞም አራቱ ሕያዋን ፍጥረታት “ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ የነበረውና ያለ የሚመጣውም
ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክ እያሉ ቀንና ሌሊት አያርፉም።” (ራዕይ 4:8)።
በእርግጥም፣ እግዚአብሔር ቅዱስ ነው፤ እናም ወደ እርሱ ስንመጣ፣ እሱን እንደዚያ ማየት
አለብን። ይህንን ማወቅ ምን ያክል ያነሳሳናል? ይህ ከራሳችን ባህሪ አንፃር በምን መንገዶች
ይፈታተነናል?
ፍቅር ምናልባት ክርስቲያኖች የእግዚአብሔርን ባህሪ ለመግለጽ የሚጠቀሙበት በጣም የተለመደው ቃል ነው። ይህ ሊሆን የሚችለው በ1ኛ ዮሐንስ 4:8 ላይ ባለው ስለ እግዚአብሔር ማንነት ከተሰጠው መግለጫ የተነሳ ሊሆን ይችላል፣ እሱም “እግዚአብሔር ፍቅር ነው” ይላል። ዮሐንስ “እግዚአብሔር አፍቃሪ ነው” አላለም፤ ይልቁንም “እግዚአብሔር ፍቅር ነው” አለ። ፍቅር የእርሱ ባሕርይ ነው፣ ህልውናው ነው። ለብዙ ሰዎች፣ ስለ እግዚአብሔር ያላቸው ምስል የሚመነጨው ሁልጊዜ የተዛባ እና ፍጹም ያልሆነ ከሆነው የፍቅር ፍቺያቸው ነው። ይልቁንም፣ የፍቅር ትርጓሜያችን በእግዚአብሔር ማንነት እና በመንፈስ አነሳሽነት በተጻፈው ቃሉ አማካኝነት ስለ ራሱ በሚገልጸው ነገር መቀረጽ አለበት። 1ኛ ዮሐንስ 4፡7-19 ስለ ፍቅር ምን ያስረዳናል?
በ1ኛ ዮሐንስ ውስጥ “በእርሱ እንድንኖር” በተደጋጋሚ በቀረበው ግብዣ ላይ
እንደተገለጸው የእግዚአብሔር ፍቅር ፍጹም፣ ነፃ እና ጥልቅ ግንኙነት ያለው ነው፤ ምክንያቱም
“እኛም እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፍቅር አውቀናል አምነንማል። እግዚአብሔር ፍቅር ነው፥ በፍቅርም የሚኖር በእግዚአብሔር ይኖራል እግዚአብሔርም በእርሱ ይኖራል።” (1ኛ
ዮሐንስ 4፡16)። እግዚአብሔር ፍቅር ነው፣ እናም ፍቅርን ለመውደድ እና ለመሻት በእርሱ
አምሳል (ዘፍ. 1፡27) ፈጥሮናል። በዕብራይስጥ፣ ለፍቅር አንድ ዋና ቃል ሔሰድ የሚለው
ነው። ይህ እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ያለውን የቃል ኪዳን ፍቅር የሚገልጸው ታማኝነትን፣
ከለላ መሆንን፣ ጽናትንና ርኅራኄን የሚገልፅ ነው።
የጥንት የዕብራይስጥ እና የግሪክ ቋንቋዎች እግዚአብሔርን ለማመልከት ብዙ የተለያዩ
ስሞችን ይጠቀማሉ፣ ይህም የእግዚአብሔርን ውብ ባህሪ የተለያዩ ገጽታዎች ለማብራራት
ነው። ከዚህ በታች ሁለት ምሳሌዎች አሉ፡-
አዶናይ፡ በቃል ኪዳኑ መሠረት ለዘላለም የሚነግሥ የሁሉም ጌታ፣ (ዘፍ. 15:2፣ መሳ.
6:15፣ ሚል. 1:6፣ መዝ. 97:5)።
ያህዌ-ይርኤ፡- ጌታ-ያዘጋጃል (ዘፍ. 22:13-14)።
በዋናነት፣ የእግዚአብሔር ፍቅር ትልቁ መግለጫ ልጁን ለዚህች ምድር መስጠቱ (ዮሐንስ
3:16) እና እርሱም ለኃጢአተኞች መሞቱ (ሮሜ 5:8) ነው። እግዚአብሔር ይህንን ከሰው ልጆች
ሊከለክለው ይችል ነበር፣ ነገር ግን እግዚአብሔር ትልቅና ጥልቅ በሆነው እና እጅግ በላቀው ፍቅሩ
ምክንያት ኢየሱስን ወደ ምድር ላከው፣ ይህም በእኛ ምትክ ሞቱ የተገለጠውን ፍቅሩን በነፃነት
እንድንመርጥ ነው። ኢየሱስ ኃጢአት በእኛና በእግዚአብሔር መካከል ላመጣው መለያየት
ድልድይ ለመሆን ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሔርን ፍጹም የፍቅር ባሕርይ (ዮሐንስ 14:9፣ ዕብ. 1:3)
ለማሳየትና ሰዎችን ሁሉ ወደ ራሱ ለመሳብ በዚህ ምድር ተመላለሰ (ዮሐንስ 12:32)።
ብዙ የእግዚአብሔር ስሞች ቅድስናውንና ፍቅሩን በዋናነት ይገልጻሉ። 1ኛ ቆሮንቶስ
13:4-8ን ያንብቡ፣ እና ሁሉንም “ፍቅር” የሚሉትን ቃላት “እግዚአብሔር” በሚለው
ይተኩ። ይህ ስለ እግዚአብሔር ባሕርይ ያለዎትን ግንዛቤ የሚያሰፋው እንዴት ነው? ስምዎን
“ፍቅር” በሚለው ቦታ ላይ ቢያስቀምጡት፣ ያ ምን ያህል ለእርስዎ ገጣሚ ይሆናል?
ምናልባት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያሉትን የመጀመሪያ ቃላት በቃላችሁ
ታውቋቸዋላችሁ፡- “በመጀመሪያ እግዚአብሔር።” በዕብራይስጥ፣ እዚህ ቦታ ላይ ያለው
የእግዚአብሔር ስም ኤሎሂም ነው። ምንም እንኳን ይህ ቃል ስለ ሐሰተኛ “አማልክት”
ሲነገርም ጥቅም ላይ ሊውል ቢችልም፣ ስለ አንድ እውነተኛ አምላክ ሲናገር፣ ከፍጥረት ሁሉ
ጋር በተያያዘ ሁሉን ቻይ የሚለው ቃል ሁሉን ቻይ ፈጣሪን ይገልጻል፤ ከእኛ ግንዛቤ በላይ
የሆነ ነገር ግን ሁሉንም ነገር የሚቆጣጠር እጅግ የላቀ አምላክን ይገልፃል። እርሱ እጅግ
ኃይለኛ ከመሆኑ የተነሳ ሲናገር አንድ ነገር ከድምፁ ብቻ ይፈጠራል።
ነገር ግን በሚቀጥለው ምዕራፍ፣ ዘፍጥረት 2፣ ለእግዚአብሔር ሌላ ስም ተሰጥቷል፡-
ያም ያህዌ የሚለው ነው። ይህ ስም ከኤሎሂም (ያህዌ ኤሎሂም)፣ ሁሉን ቻይ አምላክ ጋር
ይገናኛል፤ ነገር ግን ያህዌ የሚለው ስም የአንድ እውነተኛ አምላክ የግል ስም ሲሆን ብዙውን
ጊዜ እግዚአብሔር ከተፈጠሩት ሕዝቦቹ ጋር በፍቅር ግንኙነት የቃል ኪዳን አምላክ መሆኑን
ለማጉላት ጥቅም ላይ ውሏል።
በዘፍጥረት 1፡1 እና በዘፍጥረት 2፡7 ውስጥ ያሉትን የእግዚአብሔር መግለጫዎች ያነፃፅሩ።
ምን አስተዋላችሁ?
በዘፍጥረት 2:7 ላይ፣ እግዚአብሔር የመጀመሪያውን ሰው ከምድር ለመፍጠር በጉልበቱ
ተንበርክኮ በዓይነ ሕሊናችን መገመት እንችላለን። “እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ከምድር
አፈር አበጀው፤ በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት ሰውም ሕያው ነፍስ ሆነ።”
ይህ የሚቀርብ፣ እጅግ የሚቀርብ አምላክ ከመሆኑ የተነሳ በአዳም አፍንጫ ውስጥ የሕይወትን
እስትንፋስ እፍ አለበት። ይህ ያህዌህ የሚለው ስም ስለ እግዚአብሔር የበለጠ ቅርብ የሆነን
አምላክ ምስል ይሰጣል፤ ደግሞም ሙሴ እነዚህን ሁለት የእግዚአብሔር ባህሪያት ለእኛ ለመግለጽ
በመጽሐፍ ቅዱስ የመጀመሪያዎቹ ሁለት ምዕራፎች ውስጥ ሁለቱንም ስሞች ይጠቀማል።
እንዴት አስደናቂ ነው! እዚህ ላይ የእግዚአብሔርን ከማስተዋል በላይ ኃያል መሆን
እንደ ኤሎሂም፣ የእርሱን መገኘት፣ ከእኛ ጋር ያለውን ቅርበት ደግሞ እንደ ያህዌህ እናያለን።
እነዚህን ሁለቱንም የእግዚአብሔር ባህሪ ገጽታዎች ማሰባችን ምንኛ መልካም ነው፡-
ሁሉንም ነገር በአጠቃላይ መቆጣጠሩ እና ለእኛ ያለው ቅርበት። ጳውሎስ በማርስ ኮረብታ
ላይ ለነበሩት አቴናውያን እንደተናገረው፡- “ቢሆንም ከእያንዳንዳችን የራቀ አይደለም፤
ከእናንተ ከባለ ቅኔዎች አንዳንዶች ደግሞ፦ እኛ ደግሞ ዘመዶቹ ነንና ብለው እንደ ተናገሩ፥
በእርሱ ሕያዋን ነንና እንንቀሳቀሳለን እንኖርማለን።” (የሐዋርያት ሥራ 17:27-28)።
ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን ግንኙነት ለማሳደግ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ እግዚአብሔር
ባሕርይ በሚነግረን ላይ በመመስረት ግልጽና ሚዛናዊ የሆነ የእግዚአብሔር ምስልን ለመያዝ
መፈለግ አስፈላጊ ነው። በአንድ ክፍል ላይ ብቻ ከማተኮር ይልቅ የመጽሐፍ ቅዱስን ሁሉንም
ክፍሎች ማንበብ አስፈላጊ የሆነው ለዚህ ነው። በእርግጥም፣ ስለ እግዚአብሔር ባሕርይ
በተማርን ቁጥር፣ እሱን መውደድን እንማራለን።
ኤሊሁ በኢዮብ 36፡24-33 እና በኢዮብ 37 ውስጥ ስለ አንዳንድ የእግዚአብሔር
ባህሪያት ሲገልጽ ያንብቡ። ከዚያም እግዚአብሔር ስለ ሁሉን ቻይነቱ በኢዮብ 38 እና 39
ላይ የሰጠውን መግለጫ ያንብቡ። እነዚህ ክፍሎች ስለ እግዚአብሔር ምን ይገልፁልናል?
ክርስቲያን ላልሆኑ ሰዎች ስለ እግዚአብሔር ባሕርይ ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ መግለጫ
ለማካፈል ብትፈልጉ ከየቱ ትጀምራላችሁ?
በእርግጥ ከሁሉ የተሻለው መልስ ከኢየሱስ የሚለው ይሆናል። መጽሐፍ ቅዱስ ኢየሱስ
እግዚአብሔርን ከማንጸባረቅ በተጨማሪ እግዚአብሔርን እንደሚገልጥ ይናገራል። ይህንን
የሚያብራሩ ብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች አሉ፣ ነገር ግን በጣም በቀላሉ የሚገልፀው
ዮሐንስ 14፡9 ነው። እዚህ ላይ ኢየሱስ “እኔን ያየ አብን አይቶአል” ይላል።
እግዚአብሔር ምን እንደሚመስል የበለጠ ለማወቅ፣ ኢየሱስን መመልከት አለብን -
ቃላቱን፣ ተግባሩን፣ ባህሪውን እና በሞቱና በትንሳኤው ለሰው ልጅ ያሳየውን ታላቅ ፍቅር።
የአብ ፍቅር እና እንክብካቤ በልጁ በኢየሱስ ውስጥ በግልጽ ተገልጿል። ደስ የሚለው
መጽሐፍ ቅዱስ እርሱ ማን እንደሆነ ሙሉ ግንዛቤ እንዲኖረን በኢየሱስ ሕይወት ላይ አራት
የበለፀጉ አመለካከቶችን ሰጥቶናል። በማቴዎስ (በአይሁዳዊ የተጻፈ፣ ለአይሁድ)፣ ኢየሱስን
ለረጅም ጊዜ ሲጠበቅ የነበረው መሲህ እንደሆነ እናየዋለን። በማርቆስ ውስጥ ኢየሱስ
የአገልግሎት እና የመስዋዕትነት ሕይወት ሲኖር እናያለን። ሁልጊዜ ስለ ሌሎች ያስብ ነበር
እና ሁልጊዜም ለአባቱ ፈቃድ ምላሽ ይሰጥ ነበር። በሉቃስ ውስጥ፣ ኢየሱስ ፍጹም በሆነው
ሰብዓዊነቱ እና ርህራሄው እንዴት እንደተሰማው እናነባለን እና የምናነበው እውነት መሆኑን
ለማረጋገጥ ይህንን ጥቅስ ማንበብ እንችላለን (ሉቃስ 1:3-4)። በዮሐንስ ወንጌል ውስጥ፣ ሥጋ
የለበሰውን የእግዚአብሔር ልጅ እናያለን፤ ኢየሱስ እርሱ ነኝ ያለውን እርሱ እንደሆነ እንድናምን
ተጋብዘናል፣ ስለዚህም መንፈሳዊ ሕይወታችን እንደገና እንዲነቃቃ ይረዳናል። አራቱም
ወንጌሎች ስለ አንድ ነገር ቢናገሩም፣ “ነገሮችን በአንድ ዓይነት ዘይቤ ብቻ አይገልፁም።
እያንዳንዱ ጸሐፊ የራሱ የሆነ ተሞክሮ አለው፣ እናም ይህ ልዩነት ለተለያዩ አእምሮዎች
የሚያስፈልጉትን ነገሮች ለማሟላት የሚወጣውን እውቀት ያሰፋል እና ያጠነክራል።” — El-
len G. White manuscript 105, 1900። በቅርብ ጊዜ የትኛውን የወንጌል ክፍል አንብበዋል?
በማቴዎስ 1:23 ውስጥ ለኢየሱስ የተለየ ስም ተሰጥቶታል። ይህ የእግዚአብሔርን ባሕርይ
ለመረዳት በጣም አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው? ማቴዎስ 28:20ን ያንብቡ፣ በጥቅሱ
የመጨረሻ ክፍል ላይ ያተኩሩ። እነዚህን ሁለት ጥቅሶች ያነፃፅሩ። ምን አስተዋላችሁ?
የዚህን ስለ እግዚአብሔር ባሕርይ የሚናገረውን ጥልቅ ርዕስ በጣም በጥቂቱ ነው
የነካነው። እግዚአብሔር ከምንገምተው በላይ ታላቅ እና እጅግ አስደናቂ ነው፤ እና ለዘላለም
ስለ እርሱ እንማራለን።
እግዚአብሔር ስለማንነቱ እና በሕይወታችን ውስጥ ስላደረገው እና ስለሚያደርገው
ነገር ምስጋናችን ይገባዋል። አሁን የተወሰነ ጊዜ ወስደው ስለ እግዚአብሔር ማንነት የምስጋና
ጸሎት ያቅርቡ። ከመጽሐፍ ቅዱስ ስለ እግዚአብሔር ያወቁትን ብቻ ይግለፁ። (ለምሳሌ፣
“እግዚአብሔር ሆይ፣___________ ስለሆንክ አመሰግናለሁ፣በ ___________ ቦታ አንተ እንደነገርከኝ”)
እግዚአብሔር ሕዝቡን ባህሪውን እንዲወክሉ ጠርቷቸዋል፤
ይህንን ለማድረግ ግን እኛ በራሳችን ልናውቀው ይገባናል። ቅዱስና ፍጹም የሆኑ መንገዶቹን
በተሳሳተ መንገድ ከሚረዱት ኃጢአተኛ ዓይኖቻችን ይልቅ መጽሐፍ ቅዱስን በመመርመር
እርሱን በግልጽ ማየት በጣም የተሻለው መንገድ ነው።
“ከትውልድ ወደ ትውልድ በሰው ልብ መተላለፊያ በኩል የወረደው አባታዊ ፍቅር
ሁሉ፣ በሰዎች ነፍስ ውስጥ የተከፈተው የርኅራኄ ምንጭ ሁሉ፣ ከማይገደብና ማለቂያ
ከሌለው የእግዚአብሔር ፍቅር ጋር ሲነጻጸር ወሰን እንደሌለው ውቅያኖስና እንደ ትንሽ
ኩሬ ነው። ምላስ ሊገልጸው አይችልም፤ ብዕር ሊገልጸው አይችልም። በሕይወትዎ ውስጥ
በየቀኑ ሊያሰላስሉት ይችሉ ይሆናል፤ ለመረዳት ቅዱሳት መጻሕፍትን በትጋት ልትመረምሩ
ትችሉ ይሆናል፤ የሰማዩን አባት ፍቅርና ርኅራኄ ለመረዳት በምትጥሩበት ጊዜ እግዚአብሔር
የሰጣችሁን እያንዳንዱን ኃይልና ችሎታ ልትጠቀሙ ብትችሉ እንኳን ከዚያ በላይ የሆነና
ማለቂያ የሌለው ነው። ያንን ፍቅር ለዘመናት ልታጠኑ ትችላላችሁ፤ ነገር ግን ልጁን ለዓለም
እንዲሞት የሰጠውን የእግዚአብሔርን ፍቅር ርዝመትና ስፋት፣ ጥልቀትና ቁመት ሙሉ
በሙሉ መረዳት አትችሉም። ዘላለማዊነት ራሱ ሙሉ በሙሉ ሊገልጸው አይችልም። ሆኖም
መጽሐፍ ቅዱስን ስናጠናና በክርስቶስ ሕይወትና በድነት ዕቅድ ዙሪያ ስናሰላስል፣ እነዚህ
ታላላቅ ጭብጦች የበለጠ እየተከፈቱልን ይሄዳሉ።”—ኤለን ጂ. ኋይት፣ የቤተ ክርስቲያን
ምክሮች፣ ጥራዝ 5፣ ገጽ 740.
1. በዚህ ሳምንት የተማራችሁትን የእግዚአብሔርን ባህሪያት ስታስቡ፣ ስለ እግዚአብሔር
ባላችሁ ግንዛቤ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ያሳደረው የትኛው ነው?
2. ከእግዚአብሔር ጋር ያለዎትን ግንኙነት ለማጠናከር የትኞቹን ሌሎች የእግዚአብሔር
ባህሪያት ማጥናት ይችላሉ?
3. ከቤተሰብ አባል ወይም ከጓደኛ ጋር ወደ ክርስቶስ የሚመራ መንገድ ከሚለው መጽሐፍ
ውስጥ ምዕራፍ 1ን ያንብቡ ወይም ያዳምጡ እና አብራችሁ ተወያዩበት።