የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት መምሪያ

ለዚህ ሳምንት ጥናት የሚከተሉትን ጥቅሶች ያንብቡ፡ ዮሐንስ 15:1-8፣ ማርቆስ 1:35፣ 1 ዜና 16:11፣ መዝ. 119:105፣ ኢሳ. 50:4፣ ኢሳ. 55:1-13።
የመታሰቢያ ጥቅስ፡ “ከአፌ የሚወጣ ቃሌ እንዲሁ
ይሆናል፤ የምሻውን ያደርጋል የላክሁትንም ይፈጽማል እንጂ ወደ
እኔ በከንቱ አይመለስም።” (ኢሳይያስ 55:11)።
የመጀመሪያው መጽሐፍ ቅዱስዎ መቼ በእጅዎ እንደገባ ያስታውሱ። ምናልባት ልጅ
ሆነው ክርስቲያን በሆነ ዘመድዎ ተበርክቶልዎ ይሆናል። ወይም ምናልባት እርስዎ ራስዎ
ገዝተውት ይሆናል። መጽሐፍ ቅዱስዎ ምንም ያህል ለረጅም ጊዜ በእጅዎ ቢቆይ (ምናልባት
ከአንድ በላይ ሊኖርዎ ይችላል)፣ ለዚህ መጽሐፍ የሚሰጡትን ዋጋ ያስቡበት። እጅግ ውድ ከሆኑ
ንብረቶችዎ መካከል አንዱ ነው ወይስ ሕያው የእግዚአብሔር ቃል በእጅዎ መገኘቱ ከብዶ
አይታይዎትም? ሲያነቡ ወጥነት እያጡ ተቸግረዋል? ይህን መጽሐፍ ከየት ጀምሬ ላንብበው? ወደ
እግዚአብሔር ለመቅረብ እንዴት ማንበብ እችላለሁ? ብለው ጠይቀው ያውቃሉ?
ማርቲን ሉተር እንዲህ ብሏል፣ “ለተወሰኑ ዓመታት መጽሐፍ ቅዱስን በየዓመቱ
ሁለት ጊዜ አንብቤያለሁ። መጽሐፍ ቅዱስ ትልቅና ግዙፍ ዛፍ ቢሆንና ቃላቶቹም ትናንሽ
ቅርንጫፎች ቢሆኑ፣ እዚያ ውስጥ ምን እንዳለና ምን እንደሚሰጠኝ ለማወቅ በጉጉት
ሁሉንም ቅርንጫፎች እነካ ነበር።”
በየቀኑ የሚያድግ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ጊዜ ቢኖርዎ ወይም መጽሐፍ ቅዱስዎ
በአብዛኛው በመጽሐፍ መደርደሪያ ላይ ተዘግቶ የሚቆይ ቢሆን፣ እውነታው ግን ሁላችንም
ከእግዚአብሔር ጋር ጠንካራ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ጊዜ ማዳበር የምንችል መሆናችን
ነው። በዚህ ሳምንት የእግዚአብሔርን ቃል በተሻለ ሁኔታ ለማጥናት አንዳንድ ተግባራዊ
መንገዶችን እንመረምራለን።
*ለሚያዝያ 24 ሰንበት ለመዘጋጀት የዚህን ሳምንት ትምህርት ያጥኑ።
መጽሐፍ ቅዱስዎን ለማጥናት አላርምዎን ከወትሮው ትንሽ ቀደም ብለው ሞልተው ያውቃሉ? ከአልጋዎ ተጎትተው ተነስተው ሰዓቱን ሲመለከቱ “ቀኑን ከመጀመሬ በፊት አስራ አምስት ደቂቃ አለኝ” ብለው አስበው ብፈጥን ይሻለኛል! አጭር ጸሎት ወይም አንድን ምዕራፍ መለስ ብለው በማንበብ፣ ህሊናዎ ተረጋግቶ ነገር ግን ልብዎ በውጤቱ ሳይረካ የቀረበት ጊዜ አለ?
“ቅዱሳት መጻሕፍትን በጥድፊያ በማንበብ ምንም ጥቅም አይገኝም። አንድ ሰው
በውስጥ ውበቱን ሳያይ ወይም ጥልቅ እና የተሰወረ ትርጉሙን ሳያስተውል መጽሐፍ ቅዱስን
ከመጀመሪያው ገፅ እስከ መጨረሻው ገጽ ሊያነብ ይችላል።” ኤለን ጂ. ኋይት፣ ወደ ክርስቶስ
የሚመራ መንገድ፣ ገጽ 84
መጽሐፍ ቅዱስን ከማንበብ የሚመጡ በረከቶች በእርግጥ ቢኖሩም - ልክ እንደ እሳት
ማጥፊያ ውሃ (ብዙ እና ፈጣን) - መጽሐፍ ቅዱስን በፍጥነት በማንበብ ብዙ ነገር አለመረዳት
ቀላል ነው። እግዚአብሔር በመንፈስ አነሳሽነት የተነገረውን እና ውድ ቃሉን የሰጠን ስለ እርሱ
የበለጠ እንድናውቅ (እና በሂደቱም ስለራሳችንም የበለጠ እንድናውቅ) ነው። የማይገለጽ፣
የሚያምር የእግዚአብሔርን ባህሪ እና በታሪክ ውስጥ ወደ ሰው ልጆች የቀረበባቸውን
መንገዶች ለማየት ጊዜ ስንወስድ፣ እሱን የበለጠ እንወደዋለን። እርሱ የሰራው ሥራ መዝገብ
በእጃችን ነው - ነገር ግን ቃሉን በማንበብ እግዚአብሔርን ለማወቅ ጊዜ ማግኘት እና ጊዜ
መውሰድ አለብን (የሐዋርያት ሥራ 17:11)። የሚከተሉትን ሀሳቦች አስቡባቸው፡-
እግዚአብሔር በልባችሁ ውስጥ ለቃሉ ፍላጎት እንዲያኖር ጠይቁት። በኤርምያስ 29:13
እና በመዝሙር 37:4 ውስጥ ያሉትን የተስፋ ቃላት መሠረት አድርጋችሁ ጠይቁ። ከወትሮው
ቀደም ብሎ እንዲያነቃችሁ ወይም በቀን ውስጥ የተወሰነ ጊዜ ነፃ እንዲያደርግላችሁ ጠይቁት።
ጊዜዎን ለእግዚአብሔር ያስረክቡ። አዎ፣ ስራ በዝቶባችኋል፣ እና ብዙ አስቸኳይ ነገሮች
አሉ። ነገር ግን ከእግዚአብሔር ጋር ጊዜ ማሳለፍ በዋጋ ሊተመን የማይችል ነው። ብቻዎትን
ጸጥ ወዳለ ቦታ ይሂዱ እና መዝሙር 46:10ን ያንብቡ። “ለየሱስ አስረክባለሁ” የሚለውን
መዝሙር ለእግዚአብሔር ዘምሩ። ሊሰጡ የማይችሉትን የሕይወት ዘርፎች ያስቡ እና
ለእግዚአብሔር ያቅርቡ።
በማይፈልጉበትም ጊዜ እንኳ ከእግዚአብሔር ጋር ጊዜ ያሳልፉ። ጤናማ ለመሆን
በማስተዋል መምረጥ እና የድርጊት እቅድ እንደሚያስፈልግ ሁሉ (ልምምድ ያድርጉ፣ በደንብ
ይመገቡ)፣ ከእግዚአብሔር ጋር የጠበቀ ግንኙነት ለመመሥረትም በማስተዋል መምረጥ
ያስፈልጋል። አዳዲስ ልማዶች ለመለመድ ቢያንስ 21 ቀናት ሊፈጅባቸው እንደሚችል
ያስታውሱ፣ እናም ያለ መንፈስ ቅዱስ እርዳታ በፍፁም ስኬታማ መሆን አንችልም።
እንደገና ዮሐንስ 15:1-8ን ያንብቡ። ኢየሱስ በእርሱ ስለመኖር ምን እየነገረን ነው? እና
ይህ ለእምነታችን በጣም አስፈላጊ የሆነው ለምንድነው?
ኢየሱስ በሁሉም ነገር ፍጹም ምሳሌያችን ነው፣ እና የግል አምልኮን በተመለከተም የተለየ አይደለም። ማርቆስ 1:35 ኢየሱስ ከአባቱ ጋር ስለነበረው ጊዜ ምን ይነግረናል? ምንም እንኳን ይህ አንድ ጥቅስ ብቻ ቢሆንም፣ እዚህ ከኢየሱስ አርአያነት ብዙ መማር እንችላለን። ፀሐይ ከመውጣቷ ከረጅም ጊዜ በፊት፣ ከአባቱ ጋር ለመሆን ጸጥ ባለ ብቸኛ ቦታ ለመሆን ሄደ (ራሱን ከዕለት ተዕለት የሕይወት ግርግር አስወገደ)። ኢየሱስ በዙሪያው ያለው ዓለም ከመንቃቱ በፊት በገሊላ ባሕር ዳር ወይም በተራራ ዳር ተቀምጦ ከአባቱ ጋር ሲነጋገር የነበረውን ሁኔታ መገመት ትችላላችሁ? ይህ ጥቅስ ኢየሱስ ለጸሎት ያለውን ቁርጠኝነት እያሳየ ለእርሱ ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ እንደነበር በግልጽ ያሳያል። ይህ ጊዜ እርሱ የተጋፈጠውን ሁሉ እንዲቋቋም ብርታት የሰጠው መሆኑ አያጠራጥርም። ኢየሱስ እያንዳንዱን ቀን ለመጀመር ይህ የሚያስፈልገው ከሆነ፣ እኛስ ምን ያህል የበለጠ ያስፈልገን? እግዚአብሔር “ፊቴን ፈልጉ” ይለናል፣ እናም ምላሻችን “ጌታ ሆይ፣ ፊትህን እሻለሁ” የሚል እንደሚሆን ተስፋ ያደርጋል (መዝ.27፡8)። 1ኛ ዜና 16፡11 ፊቱን እንዴት መፈለግ እንዳለብን የሚነግረን ምንድነው?
በየጠዋቱ ከእግዚአብሔር ጋር ለመሆን የሚሄዱበት ቦታ አለዎት? ምናልባት በየቀኑ
ከኢየሱስ እግር አጠገብ ተቀምጠው የእግዚአብሔርን ቃል መማር የሚችሉበት በመስኮት
አጠገብ ያለ ወንበር፣ ከቤት ውጭ ጸጥ ያለ ቦታ ወይም የወጥ ቤት ጠረጴዛ እንኳን ሊያገኙ
ይችላሉ። በኢየሱስ እግር አጠገብ መቀመጥ በጣም መልካሙ ቦታ ነው (ሉቃስ 10:39-42)።
ከእግዚአብሔር ጋር ጊዜ ለማሳለፍ ወደ አንድ የተወሰነ ቦታ የመሄድ የዕለት ተዕለት ልማድ
በመፍጠር፣ በየቀኑ ወደዚያ የመመለስ ዕድላችን እንዲሰፋ ያደርጋል። ድንገተኛ ሁኔታዎች
ስለሚከሰቱ እና ከእግዚአብሔር ጋር ጊዜ ማሳለፍ ላይችሉ ስለሚችሉ እዚህ ወይም እዚያ
አንድ ቀን ሲያመልጥዎት ተስፋ አይቁረጡ። ነገር ግን ከእግዚአብሔር ጋር ጊዜ ሳያሳልፉ ብዙ
ቀናት፣ ሳምንታት ወይም ወራት እንዳያልፉ ይጠንቀቁ። ከእግዚአብሔር ጋር የሚኖር ዘላቂ
ግንኙነት የዕለት ተዕለት ውሳኔ መሆኑን ያስታውሱ፣ ከፈለጉ ዛሬ እንደገና መጀመር ይችላሉ።
ባለፈው ሳምንት፣ በጸሎት እና በመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ምን ያህል ጊዜ አሳለፉ? መልስዎ
ቅድሚያ በሚሰጧቸው ነገሮች ማድረግ ስላለብዎ ለውጦች ምን ይነግርዎታል?
መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት የግድ ምሁር መሆን ባይኖርብንም፣ መጽሐፍ ቅዱስን በጥልቀት ማጥናት የምንችለው እንዴት ነው?
መፀለይ፡ መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት ስንመጣ ፀሎት እጅግ አስፈላጊ ከመሆኑ የተነሳ
የጸሎትን አስፈላጊነት ከልክ በላይ መግለጽ አይቻልም። ኤለን ጂ. ኋይት መጽሐፍ ቅዱስን
ለማንበብ ስንመጣ ብቻችንን እንዳልሆንን ትናገራለች። መንፈስ ቅዱስ መሪያችን እንዲሆን
በመጋበዝ፣ ሌሎች ትኩረት የሚከፋፍሉ ነገሮችን ሁሉ እንቃወማለን፤ ጠላትም ይሸሻል።
“መጽሐፍ ቅዱስ ያለ ጸሎት ፈጽሞ ሊጠና አይገባውም። መንፈስ ቅዱስ ብቻውን ለመረዳት
ቀላል የሆኑ ነገሮችን አስፈላጊነት እንድንረዳ ወይም ለመረዳት አስቸጋሪ የሆኑ እውነቶችን
ከመጋፈጥ ሊያድነን ይችላል።” ታላቁ ተጋድሎ፣ ገጽ 599፣ 600
ማንበብ እና መፃፍ፡ መጽሐፍ ቅዱስን እንዲሁ ከላይ ከላይ በማንበብ እና በማጥናት
መካከል ያለው ዋና ልዩነት መጻፍ ነው። መጻፍ ሀሳባችንን ለማረጋጋት፣ የእግዚአብሔርን
ቃል ለማሰላሰል እንዲሁም አጢነን፣ ትርጓሜ ሰጥተን፣ አተገባበሩን አስበን ቁርጠኛ
እንድንሆን በሚያስችል ፍጥነት እንድንሄድ ይረዳናል።
እንዲሁም የመጀመሪያዎቹ የተበታተኑ ሀሳቦቻችን ከጭንቅላታችን ወጥተው ወደ
ብዕራችን እና ከዚያም በልባችን ውስጥ እንዲሰሩ ይረዳል። የጻፍነውን ነገር ለማስታወስም
የበለጠ እድል አለን (መዝ. 119:15, 16)።
መጻፍ ካልቻሉ፣ መጽሐፍ ቅዱስን ጮክ ብለው ለማንበብ (ወይም ለማዳመጥ) ይሞክሩ፣
ከዚያም ወደ እግዚአብሔር ለመጸለይ ይሞክሩ።
ማጋራት፡ የተማርነውን ለአንድ ሰው እንንገር። ይህ በአእምሯችን ውስጥ እንዲጠነክር
እና ሌላ ሰውን ለማበረታታት ይጠቅማል። ለመጀመር አጭር የመጽሐፍ ቅዱስ መጽሐፍን
(እንደ ዮናስ፣ ማርቆስ፣ ፊልጵስዩስ ወይም 1ኛ ዮሐንስ ያሉትን) እንምረጥና ቀስ በቀስ
እንቀጥል። ለአንድ ጥቅስ (በቁጥር-በቁጥር ዘዴ)፣ ለአንድ አንቀፅ ወይም ለአንድ ሙሉ
ምዕራፍ ተግባራዊ ማድረግ የምንችልባቸው ቀላል አቀራረቦች እነሆ፡
1.
መንፈስ ቅዱስ አእምሯችንን እንዲመራ እና ስናነብ ልባችንን እንዲያለሰልስ
እንጸልይ።
2. የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ወይም ክፍል እንምረጥ።
3. አንድን ጥቅስ በምናነብበት ጊዜ ጎልተው የሚታዩትን ክፍሎች በማስታወሻ ደብተር
እንፃፈው።
4. በጸሎት ምንባቡን እንደገና እናንብብ እና ቁልፍ ሐሳቦቹን እናስምርባቸው።
5. የተሰመሩባቸው ሐሳቦች የሚነግሩንን እንጻፋቸው።
6. ስለ እነዚህ ሐሳቦች እና ከእግዚአብሔር ጋር ስላለን ግንኙነት እንጸልይ።
7. ይህንን ዛሬ ለማን እንደምናጋራው እናስብ።
“የእግዚአብሔር ሕዝብ በጸጋ ሲያድጉ፣ ዘወትር ስለ ቃሉ የበለጠ ግልጽ የሆነ ግንዛቤ እያገኙ
ይሄዳሉ። በቅዱስ እውነቶቹ ውስጥ አዲስ ብርሃንና ውበትን ያስተውላሉ። ይህ በሁሉም ዘመናት
በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ እውነት ሆኖ ቆይቷል፣ እናም እስከ መጨረሻው ይቀጥላል።” El-
len G. White, Counsels to Writers and Editors, pp. 38, 39
ከላይ በተጠቀሰው ጥቅስ ውስጥ ያለው መልእክት ለእርስዎ እውነት ሆኖ ያገኙት በምን
መንገድ ነው? መዝሙር 119:105ን ያንብቡ።
መጽሐፍ ቅዱሳችንን ማጥናት የምንችልባቸው ብዙ መንገዶች አሉ፣ ለምሳሌ የጥቅስ- በጥቅስ ዘዴ (አስቀድሞ የተጠቀሰው)፣ የምዕራፍ ጥናት፣ የርዕስ ጥናት፣ የቃላት ጥናት ወይም የመጽሐፍ ጥናት። በማጣቀሻ እና በመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ማጥናት እንችላለን፤ እና ተጨማሪ ግንዛቤ ለማግኘት መጽሐፍ ቅዱስን ከዘመናት ተጋድሎ ተከታታይ መጽሐፎች (የሐይማኖት አባቶችና ነቢያት፣ ነቢያትና ነገስታት፣ የዘመናት ምኞት፣ የሐዋርያት ሥራ፣ ታላቁ ተጋድሎ) ጋር ማንበብ እንችላለን። በተፈጥሮ ውስጥ ወደ ውጭ ወጥተን መጽሐፍ ቅዱስ ሲነበብ ማዳመጥ ወይም ከጓደኞች ወይም ከትንሽ ቡድን ጋር አብረን ማጥናት እንችላለን። ከሰዎች ጋር ያለንን ጓደኝነት/ግንኙነት በተለያዩ መንገዶች እና በአዲስ ተግባራት ሕያው ለማድረግ እንደምንሠራ ሁሉ መጽሐፍ ቅዱሳችንን ስናጠና የተለያዩ ዘዴዎችን በመጠቀም ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን የዕለት ተዕለት ቀጠሮ ትኩስ እና ሕያው ማድረግ አለብን። ሁልጊዜም የምንማራቸው ብዙ ነገሮች አሉ! የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ጊዜዎን ሕያው ለማድረግ የሚረዳ አንድ ነገር የተረዳነውን ለሌሎች ማካፈል ነው። የተማርነውን ስናብራራ፣ የማጠቃለል እና የማዋሃድ ሂደቱ ሀሳባችንን ያጠነክረዋል። ይህ እውቀትን አጥብቀን እንድንይዝ ይረዳናል። ድርቡ በረከት ከሌሎች ጋር ስንካፈል እና ስንወያይ፣ መንፈሳዊ ውይይቱ ብዙውን ጊዜ እኛንም የሚሰሙንንም ይገዳደራል፤ ያጠነክራልም። ብዙውን ጊዜ ጥልቅ ትምህርት በአእምሯችን ውስጥ የሚከሰተው ለሌሎች ስናካፍል ወይም ስናስተምር ነው። እንዲሁም በየቀኑ የምታጠኑት ነገር ለእናንተ የእግዚአብሔር መልእክት ብቻ ሳይሆን ለሌሎችም መልእክት መሆኑን ትገነዘባላችሁ። ኢሳይያስ 50:4ን ያንብቡ። ይህ ጥቅስ ከእግዚአብሔር ጋር ስለሚኖር ግንኙነት እና ያ ደግሞ ከሌሎች ጋር ያለንን ግንኙነት እንዴት እንደሚነካ ምን ይነግረናል?
የግል የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ጊዜያችን እኛን የሚያጠነክር ብቻ ሳይሆን በዚያ ቀን
የምናገኛቸውን ሌሎች ሰዎች እንድናበረታታ ያስችለናል። ድርብ በረከት የሚሆነውም ለዚህ
ነው።
መንፈሳዊ ሕይወታችን ማራቶን ነው። ጌታ ሩጫችንን በጽናት እንድንሮጥና ዓይናችንን
በግቡ ላይ አተኩረን መቀጠል እንድንችል እንዲያስችለን እንጠይቀው (ፊልጵ. 3:14)።
ለተወሰነ ጊዜ ትንሽ ቸልተኛ ሆነው ከነበረ ተስፋ አይቁረጡ፤ ነገር ግን ግንኙነታችሁን፣
በተለይም የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት እና የጸሎት ጊዜዎትን ሕያው ለማድረግ አስፈላጊ ለውጦች
ያድርጉ። በእውነትም ዛሬ እግዚአብሔርን ማወቃችን የዘላለም ሕይወት ነው (ዮሐንስ 17:3)።
በእርሱ እና በቃሉ ውስጥ ለመኖር ያለን ዕለታዊ ቁርጠኝነት ሕይወታችንን የሚቀይር ነው።
የዚህን ሳምንት መሪ ጥቅስ ያንብቡ እና ትርጉሙን ያስቡበት። በአሁኑ ጊዜ ምን እያጠኑ
ነው? ይህንን ከማን ጋር ሊካፈሉ ይችላሉ?
ስለሚወዱት ጣፋጭ ምግብ ያስቡ። ለጤናዎ ጥሩ ነው? ምናልባት ማርን ወይም ደግሞ
የጣዝማ ማርን ለመድኃኒትነት ጥቅም ሊጠቀሙበት ይችሉ ይሆናል። የማር ወለላ ሞክረው
ከሆነ፣ ለስላሳው በምላስዎ ላይ ሲቀልጥ ምን ያህል ጣፋጭ እንደሆነ ያውቃሉ።
በመዝሙር 119፡103፣ 104፣ መጽሐፍ ቅዱስ ራሱን ለመደሰት ምክንያት እንደሆነ የማር
ወለላ ይገልጸዋል ፡- “ቃልህ ለጕሮሮዬ ጣፋጭ ነው፤ ከማርና ከወለላ ይልቅ ለአፌ ጣፈጠኝ።
ከትእዛዝህ የተነሣ አስተዋልሁ”
“ከትእዛዝህ የተነሣ አስተዋልሁ” ማለት ምን ማለት ነው? (መዝ. 119፡104)። ይህ
ሀሳብ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ለእኛ ምን እንደሚያደርግልን ለመረዳት አስፈላጊ የሆነው
ለምንድን ነው?
አዎ፣ ዓለም ከሚያቀርበው ከማንኛውም ነገር በተለየ የእግዚአብሔር ቃላት ለነፍሳችን
በእርግጥ ጣፋጭ ናቸው። ከብዙ ጣፋጭ ምግቦች በተለየ፣ የእግዚአብሔር ቃል ጣፋጭነት
ለነፍሳችን ፈውስ የሚሰጥ እና ባህሪያችንን የሚቀይር ነው። ከእግዚአብሔር ርቀው ከነበረ፣
በጉልበቶችዎ ተንበርክከው ቃሉን መክፈትና ብቻውን የሚያረካውን የሕይወት ውሃ
መጠጣት ይችላሉ።
በኢሳይያስ 55:1-13 ላይ፣ ነቢዩ ከላይ የተጠቀሰውን መልእክት ያሰፋዋል። ይህንን
ምዕራፍ በማንበብ ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ ይስጡ፡
ጌታ ወደ እርሱ ለሚመጡት ከቃሉ “እንዲበሉ” ምን ይሰጣቸዋል?
እዚህ ላይ ለእርስዎ የሚያቀርበው ግብዣ ምንድን ነው? ፈተናው ምንድን ነው? የተስፋ
ቃሉስ ምንድን ነው?
የእግዚአብሔር ሕያውና ኃይለኛ ቃል በክርስቶስ እንድናድግ ሲገዳደረን ወደ ልባችን፣
አእምሯችን እና ነፍሳችን በቀጥታ ይዘልቃል። ነገር ግን ይህንን ለእኛ ሊያደርግልን የሚችለው
ጊዜ በሰጠነው ፣ ራሳችንን ለማስገዛት፣ ትሁት ለመሆን እና የሚያስተምረውን ለመከተል
ፈቃደኛ ለመሆን በጣርን መጠን ነው (አዎ፣ ጥረት የሚጠይቅ ነው) ።
“እግዚአብሔር በሚገኝበት ጊዜ መፈለግ”(ኢሳ. 55፡6) የምንችልባቸው ተጨባጭ
መንገዶች ምንድን ናቸው?
የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ዓላማ እግዚአብሔርን ማወቅ እና
ከእርሱ ጋር ባለን ግንኙነት ማደግ ነው፣ ምክንያቱም የዘላለም ሕይወት ማለት ከምንወደው
አምላካችን ጋር መሆን ስለሆነ ነው (ዮሐንስ 5:39፣ ዮሐንስ 17:3)። የማንኛውም ግንኙነት
አካል የጋራ ተሳትፎ ነው። በራዕይ 3:20 ላይ ኢየሱስ ይህንን ከእኛ ጋር ለማድረግ
እንደሚፈልግ እናነባለን፤ ነገር ግን ፍጡራን እንደመሆናችን ስለ ፈጣሪያችን የበለጠ
እየተማርን እንደምንቀጥል መገንዘብ አለብን። እንደ ውድ ዕንቁዎች ቆፋሪ፣ በመጽሐፍ
ቅዱስ ውስጥ ዘወትር እርሱን መፈለግ አለብን። የተወሰኑ ታሪኮችን ወይም የመጽሐፍ
ቅዱስ ክፍሎችን ደጋግመን አንብበን የነበርን ብንሆንም ሁልጊዜ አዲስ የሚሆኑብን ብዙ
ነገሮች አሉ። “የአዕምሮ እድገት ደረጃችን ምንም ይሁን ምን፣ ለበለጠ ብርሃን ጥልቅ እና
ቀጣይነት ያለው ቅዱሳት መጻሕፍትን መመርመር እንደማያስፈልግ ለአፍታ እንኳን ልናስብ
አይገባንም። እንደ ሕዝብ፣ የትንቢት ተማሪዎች እንድንሆን በተናጠል ተጠርተናል።” Ellen
G. White, Counsels to Writers and Editors, p. 41።
እንዲሁም መጽሐፍ ቅዱስን ከራሳችን አእምሯዊ አስተያየት ወይም ሀሳብ ጋር አስማምተን
ለማስኬድ መሞከር የለብንም። “ቅዱሳት መጻሕፍትን የምንመረምረው እንዴት ነው?
አስተምህሮአችንን አንድ በአንድ ይዘን ቅዱሳት መጻሕፍት ሁሉ ከተቋቋሙት አስተያየቶቻችን
ጋር እንዲስማሙ ለማድረግ እንሞክር? ወይስ ሀሳቦቻችንንና አመለካከቶቻችንን ወደ ቅዱሳት
መጻሕፍት ወስደን በሁሉም አቅጣጫ ንድፈ ሐሳቦቻችንን በመጽሐፍ ቅዱስ እንለካለን? መጽሐፍ
ቅዱስን የሚያነቡ እና የሚያስተምሩ ብዙዎች የሚያስተምሩትን ወይም የሚያጠኑትን ውድ
እውነት አይረዱም። . . . ብዙዎች ለቅዱሳት መጻሕፍት ቃላት ከራሳቸው አስተያየት ጋር የሚስማማ
ትርጉም ይሰጣሉ።”— Ellen G. White, Counsels to Writers and Editors, p. 36።
1. ብዙውን ጊዜ ወደ መጽሐፍ ቅዱስ የሚቀርቡት በምን ዓይነት አመለካከት ነው?
መለወጥ የሚያስፈልገው ነገር አለ? የትሕትና አመለካከት እና ለቃሉ ራስን ማስረከብ
ጣም አስፈላጊ የሆነው ለምንድነው?
2. ቅዱሳት መጻሕፍት ስለ ራሳቸው እንዲናገሩ ለማድረግ ወደ ጎን መተው የሚያስፈልገን
እርግጠኛ የሆንንባቸው አመለካከቶች ይኖሩ ይሆን? ከሆነ፣ ስለ እነርሱ መጸለይ
መጀመር የምንችለው እንዴት ነው?
3. አንድ ሰው ከእግዚአብሔር ጋር ባለ ውጫዊ ግንኙነት ውስጥ እውነተኛነት እንቅፋት
ሊሆን የሚችለው እንዴት ነው? ማለትም፣ ሁልጊዜ አዲስ ነገር የማግኘት ፍላጎት
አንድን ሰው በተለይም ለራስ ወዳድነት ዓላማ ሊያውለው ፈልጎ ከሆነ ሊያታልለው
የሚችለው እንዴት ነው?
ማጠቃለያ፡ የግል የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ከእግዚአብሔር ጋር ሕያውና ዘላቂ ግንኙነት
ለመፍጠር ዋና ነገር ነው። የእግዚአብሔር ቃል ባለፉት መቶ ዘመናት እንዳደረገው ሁሉ፣
ለሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ሕይወታችንም ትርጉም ባለው መንገድ ይናገራል። ማንኛውንም
ወዳጅነት ሕያው ለማድረግ እንደምንሠራው ሁሉ፣ “ቃሌ … የምሻውን ያደርጋል የላክሁትንም
ይፈጽማል እንጂ ወደ እኔ በከንቱ አይመለስም” (ኢሳ. 55:11) ያለውን ቃል በመታመን፣
የአምልኮ ሕይወታችንን ሕያው ለማድረግ መንገዶችን መፈለግ አለብን።